መጽ. ሩት
ከዚኽን ቀደም በነበረው የጡመራ መድረኬ ይቀርቡ የነበሩ ተከታታይ ጽሑፎችን በዚኽ በአዲሱ መድረኬ እንዳቀርበው በርካታ ወዳጆቼ በጠየቁኝ መሠረት ቀጥሎ ለማቅረብ እሞክራለሁ። መልካም ንባብ።
መጽሐፈ ሩትን በጥንቃቄ ስናነብ አስደናቂ ታሪክና ጥልቅ ምሥጢራትን እናገኛለን። ሩት ባሏና ሁለት ወንዶች ልጆቿ በረሃብ ምክንያት ተሰደዱ። የተሰደዱት ከቤተ ልሔም ነበር። ተሰድደው የሄዱትም ወደ ሞዓብ ምድር ነበር። ኦሪት አሞናዊና ሞዓባዊ ወደ እግዚአብሔር ርስት እንዳይገቡ ትከለክላለች። እስራኤልም ከአሞናውያንና ከሞዓባውያን ጋር በጋብቻ እንዳይተባበሩ ኦሪት አግዳ ነበር።
ረሃብ እጅግ መጥፎ ነገር ነው። ክቡሩን ሰው ያዋርዳል፣ ከሰው ፊት ያቆማል፣ መልክና ዐመል ይለውጣል። ስለ ሆነም ነው አበው “እምነ ረሃብ ይኄይስ ኲናት፤ ከረሃብ ጦር ይሻላል” ያሉት። የዓለም ሕዝብ ሁሉ በዘሩ ይባረኩ ዘንድ ተስፋ ተሰጥቶት የነበረውን አብርሃምን ከአሕዛብ ነገሥታት ፊት ያቆመው ረሃብ ነው። ያዕቆብን ያኽል የበረከት ሰው በስተርጅና ማለት በ130 ዓመቱ በፈርዖን ፊት ያቀረበው ረሃብ ነው። እስራኤልን ለአብርሃም በቃል ኪዳን ከተሰጠች ምድር አውጥቶ ለግብፅ ባርነት የዳረገ ረሃብ ነው። ሩትን ከኤፍራታ (ከቤተ ልሔም) ወደ ሞዓብ ምድር እንድትሰደድ ያደረጋት ያው ክፉው ረሃብ ነው።